2013 ማርች 28, ሐሙስ

“ስለእኛ ሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” ሮሜ 8፡34 ብዙ ጊዜ ብዙ ወገኖቻችን ይህንን ጥቅስ በመያዝ ኢየሱስ ክርስቶስ አማላጅ ነው ከእርሱ ውጪ ማንም ስለእኛ እግዚአብሄርን የሚለምንልን የለም ይላሉ ቃሉም እንዲህ ሲል ይጀምራል “እግዚአብሄር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል” ይህ ማለት እግዚአብሄር ተከተሉኝ ብሎ በመጥራት የመረጣቸውን አይ እነርሱ አንተን ሊከተሉ አይገባቸውም ሊመረጡም አይችሉም ብሎ የሚከሳቸው ማን ነው ? በማለት ይጠይቃል በመቀጠልም “የሚያጸድቅ እግዚአብሄር ነው” በማለት የመረጣቸውን ሰዎች መንግስቱን ለማውረስ እናንተ የአባቴ ብሩካን ብሎ የሚያጸድቃቸው እግዚአብሄር ነው አለ እንዲሁም “ የሚኮንን (የሚፈርድ ) ማነው ” በማለት ይጠይቃል ፡፡ “መኮነን ” ከግእዙ ሳይተረጎም ቀጥታ የተወሰደ ቃል ሲሆን መኮነን ማለት መፍረድ ማለት ነው ምክንያቱም “ኮነነ” ከሚለው የግእዝ ስርወ ቃል የወጣ ሲሆን “ኮነነ” ማለት ደግሞ ፈረደ ፣ገዛ ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ማጽደቅና መኮነን የአማላጅነት ስራ ሳይሆን የፈራጅነት ስራ እንደሆነ ልብ እንበል በመቀጠልም “የሚኮንንስ ማነው ?” ብሎ ለጠየቀው ጥያቄ መልስ ሲሰጥ ቁጥር 34 ላይ “የሞተው ይልቁንም ከሙታን የተነሳው በእግዚአብሄር ቀን ያለው ” በማለት አሁን ያለበትን የእግዚአብሄርነት የስልጣን ስፍራ ይገልጻል ፡፡ የሞተውና ሞትን ድል አድርጎ በስልጣኑ የተነሳው ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሄር ቀኝ ( በእግዚአብሄርነት ስልጣን) አለ ማለት ነው፡፡ መቼም እግዚአብሄር ቀኝና ግራ ፊትና ኋላ እንደፍጡር የለውም እርሱ ስፍራ የማይወስነው ረቂቅ ነው የነፋስን ቀኝና ግራ የሚያውቅ ማነው ? ከነፋስ ይልቅ ነፍስ ትረቃለች ከነፍስ ደግሞ መላእክት ይረቃሉ ከመላእክት የበለጠ ደግሞ እግዚአብሄር ይረቃል ስለዚህ እግዚአብሄር በአለም ሁሉ ምሉእ ነው ፡፡ ታዲያ በእግዚአብሄር ቀኝ ሲል ምን ማለት ነው ? ብለን ስንጠይቅ በመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ቀኝ የተለያየ ትርጉም ቢኖረውም በዚህ ምእራፍ ላይ ግን ክብርን ፣ስልጣንን ያመለክታል ፡፡ በመዝ 117፡16 ላይ “የእግዚአብሄር ቀኝ ሃይልን አደረገች ” ይላል ይህ ማለት እግዚአብሄር በስልጣኑ ኃይልን እንዳደረገ የሚገልጽ ነው ምክንያቱም እግዚአብሄር ኃይልን የሚያደርገው ሰዎችንም ከፍ ከፍ የሚያደርገው በስልጣኑ በመለኮታዊ ኃይሉ መሆኑ ግልጽ ነው :: በመሆኑም የእግዚአብሄር ቀኝ ሲል ስልጣኑን (መለኮታዊ ክብሩን ) ያመለክታል፡፡ በዘጸ 15፡12 ላይ “ቀኝህን ዘረጋህ ምድርም ዋጠቻቸው ” ይላል ከዚህም የምንረዳው ግብጻውያንን እግዚአብሄር በስልጣኑ ምድር እንድትውጣቸው ማድረጉን ነው፡፡ ስለዚህ “በእግዚአብሄር ቀኝ ያለው ” ማለቱ በስልጣንና በክብር በሰማያት ያለው ማለቱ ነው፡፡ ይህም ማለት ክርስቶስ ቀድሞ ስጋ ከመልበሱ በፊት ክብር የሌለው ሆኖ በኋላ ክብር አገኘ ለማለት አይደለም ክብርና ስልጣኑ ቅድመ ተዋህዶ ጊዜ፣ ተዋህዶ ፣ድህረ ተዋህዶ ከባህርይ አባቱ ከአብ ከባህርይ ህይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ትክክል ነው ፡፡ በመቀጠል እንዲህ ይላል “በእግዚአብሄር ቀኝ ያለው ደግሞም ስለእኛ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው ” በክፍት ቦታው ላይ ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን ሙሉ ብንባል ያለጥርጥር የምንሞላው የሚፈርደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው የሚለውን ነው፡፡ ምክንያቱም ከላይ በዝርዝር እንዳየነው ጥቅሱ የሚያመለክተው ፈራጅነቱን እንጂ አማላጅነቱን በፍጹም አይደለም ፡፡ ማጽደቅና መኮነን ከቻለ እንዲሁም በእግዚአብሄር ቀኝ (ክብር) ካለ እርሱ ክርስቶስ ፈራጅ እንጂ አማላጅ አይሆንም፡፡ ደግሞ “የሚኮንን ማነው ?” የሚለውና “ስለእኛ የሚማልደው ” የሚሉት ሁለት ቃላት (ሃሳቦች) እርስ በእርሳቸው እንዳይጋጩ አስማምቶ መተርጎም ያስፈልጋል፡፡ ሌላው ልንረዳ የሚያስፈልገው ነጥብ “የሚኮንንስ ማነው የሞተው ይልቁንም ከሙታን የተነሳው በእግዚአብሄር ቀኝ ያለው ደግሞ ስለእኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው ” ያለው ለትስብእት ነው ምክንያቱም ትስብእት (ስጋ) መለኮት ስለተዋሃደ ቢሞትም ከሞት በሃይል ተነሳ መነሳት ብቻም አይደለም የመለኮት ገንዘብ ለስጋ ገንዘቡ ስለሆነ እግዚአብሄርነትን አግኝቶ አሁንም በእግዚአብሄር ቀኝ ማለትም በእግዚአብሄርነት ክብር አለ ደግሞም ስለእኛ ይማልዳል እዚህ ላይ ልብ እንበል ስለእኛ የሚማልደው ሲል አሁን ስጋ በሰማይ የተዋሃደውን መለኮት እየወደቀ እየተነሳ እያነባም የሚማልድ የሚለምን ነው ማለት አይደለም በስጋው ወራት ማለትም በዚህች ምድር በፈጸመው የአንድ ጊዜ ልመና አሁንም ድረስ የሚያድን መሆኑን ሚገልጽ ነው ፡፡ አንዳንድ ሰዎች “ስለእኛ የሚማልደው ” የሚለውን ቃል ይዘው አሁንም እየወደቀ እየተነሳ የሚማልድ ነው ብለው የሚያስቡ አሉ …አይደለም የመስቀሉን ምልጃ ነው አሁን የሚደረግ አስነስሎ የጻፈው ፡፡ ለምሳሌ ጌታ ከመወለዱ ከ 700 አመታት በፊት የነበረው ኢሳይያስ በትንቢቱ መጽሃፍ ላይ ስለጌታ የእለተ አርብ እንግልት ሲጽፍ እንዲህ አለ “ከአመጸኖች ጋር ተቆጥሯል ….ስለአመጸኖች ማለደ ” ይላል ኢሳ 53፡12 አሁን ይህን ቃል ስንመለከተው ያለፈ ድርጊት ነው እንጂ ወደ ፊት የሚፈጸም ድርጊት አይመስልም ኢሳይያስ ግን በዘመኑ እየተናገረ ያለው ወደፊት ከ 700 አመታት በኋላ ጌታ ላይ ስለሚደርሰው መከራና የማዳን ስራ ነበር፡፡ ቅዱስ ዳዊትም “እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ አጥንቶቼ ሁሉ ተቆጠሩ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም ልብሶቼንም ለራሳቸው ተከፋፈሉ በቀሚሴም ላይ እጣ ተጣጣሉ ” ይላል ፡፡ መዝ 21፡16-18 መዝሙረኛው ዳዊት በዘመኑ ወደፊት ሚሆነውን እንደ ክርስቶስ ሆኖ ይናገር ነበር ከ 800 አመት በኋላ ሚሆነውን የጌታ ስቃይ እርሱ ግን እንደሆነ አድርጎ መግለጹ ስህተት እንዳልሆነ ሁሉ የተፈጸመውን ወደፊት እንደሚፈጸም አድርጎ ቅዱስ ጳውሎስ “ስለእኛ የሚማልደው ” ብሎ ቢገልጸውም ትክክልና የመጽሃፍ ቅዱስ ዘይቤ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል ፡፡ ከዚህ ውጪ ግን ዛሬም ክርስቶስ በሰማይ እየወደቀ እየተነሳ ይማልዳል ብሎ ማሰብ በዚህ ምድር ላይ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የፈጸመውን የማዳን ስራ እንዳልተሟላ በሰማይም የሚቀጥል አድርጎ መቁጠር ነው፡፡ ይህንን እንዳንል ደግሞ ክርስቶስ እራሱ በመስቀል ላይ በመጨረሻው ሰአት ላይ “ተፈጸመ ” ብሏል ፡፡ ዮሃ 19፡ 30 ቅዱስ ጳውሎስም በ2ኛ ቆሮ 5፡16 ላይ “ክርስቶስን በስጋ እንደሆነ ያወቅነው እንኳን አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ በስጋ አናውቀውም ” ብሏል ይህም ማለት ክርስቶስ ስጋን እንደተዋሃደ ቢያርግም አሁን ግን በስጋ የሚማልድ ፣ሚወድቅ፣ የሚነሳ በምድር ላይ ሲያደርግ እንደነበረው የሚያነባ አይደለም በክብር ዙፋኑ ተቀምጦ የሚፈርድ ነው እንጂ፡፡ መጽሃፍ እንዲህ ይላል “ሁላችን በክርስቶስ ፍርድ ወንበር ፊት እንቆማለን” ሮሜ 14፡10 “ሁላችን በክርስቶስ በፍርድ ወንበር ፊት ልንገለጥ ይገባናል ”2 ቆሮ 5፡10 ፣ዮሃ 5፡ 22 “ፍርድን ሁሉ ለወልድ ሰጠው ” ክርስቶስ ከእርገቱ በኋላ በምድር ሲያደርግ እንደነበረው የመለመን ፣የመማለድ አገልግሎት እንደማይፈጽም እንዲህ ሲል ተናግሯል “እኔም ስለእናንተ አብን እንድለምን የምላችሁ አይደለሁም ፡፡” ዮሃ 15፡25 ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ይፈርዳል እንጂ አይማልድም፡፡ ነገር ግን ብዚህ መልኩ መጽሃፍን ካልተረዳን "ይማልዳል" የሚል ቃል የያዙ በመሆናቸዉ ብቻ አማላጅ የሚል ትርጉም ከሰጠን ወደ አልሆነ ምንፍቅና ይወስደናልና እንጠንቀቅ። ለዚህ ማስረጃ የሚከተሉትን ጥቅሶች መመልከት ይቻላል:- ሮሜ ምዕራፍ 8፡ 26 – 27 እንዲሁም ደግሞ መንፈስ ድካማችንን ያግዛል፤ እንዴት እንድንጸልይ እንደሚገባን አናውቅምና፥ ነገር ግን መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት ይማልድልናል፤ ልብንም የሚመረምረው የመንፈስ አሳብ ምን እንደ ሆነ ያውቃል፥ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ስለ ቅዱሳን ይማልዳልና። /ግንዛቤ መንፈስ ቅዱስ ይማልድልናል/ ሮሜ 8፡34 የሞተው፥ ይልቁንም ከሙታን የተነሣው፥ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለው፥ ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው። /ግንዛቤ ኢየሱስ ይማልዳል/ ኤር 7 ፡23-25ነገር ግን። ቃሌን ስሙ፥ እኔም አምላክ እሆናችኋለሁ እናንተም ሕዝብ ትሆኑኛላችሁ፤ መልካምም ይሆንላችሁ ዘንድ ባዘዝኋችሁ መንገድ ሁሉ ሂዱ ብዬ በዚህ ነገር አዘዝኋቸው። ነገር ግን በክፉ ልባቸው አሳብና እልከኝነት ሄዱ ወደ ፊትም ሳይሆን ወደ ኋላቸው ሄዱ እንጂ አልሰሙም ጆሮአቸውንም አላዘነበሉም። አባቶቻችሁ ከግብጽ ምድር ከወጡበት ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ፥ በየዕለቱ እየማለድሁ ባሪያዎቼን ነቢያትን ሁሉ ልኬባችሁ ነበር። /ግንዛቤ እግዚአብሔርም ይማልዳል/ እነዚህን ሦስቱንም ኃይለ ቃሎች አስማምተንና አስታርቀን ለመጠቀም እንድንችል በጸሎታችን ማለት የሚገባን አብ ፣ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አማልዱን ማለት ሊያስፈልግ ይመስላልና ።ይህ ደግሞ ታላቅ ስህተት ነዉ።ስለዚህ አንድ ቃል በመያዝ ድምዳሜ ላይ መድረስ ይብቃ እንላለን። ወስብሃት ለእግዚአብሄር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይትአኮት ወይሴባህ ስሙ ለእግዚአብሄር ወትረ በኩሉ ጊዜ ወበኩሉ ሰአት አሜን።

1 አስተያየት:

  1. ኢየሱስ አማላጅ እንደሆነ አውቀሀል የማርያም አታማልድም ታማልዳለች የሚል ቦታ ስጤኝ

    ምላሽ ይስጡሰርዝ